አሞራውያን
ከWikipedia
አሞራውያን (ሱመርኛ፦ ማርቱ፤ አካድኛ፦ አሙሩ፤ ግብጽኛ፦ አማር፣ ዕብራይስጥ፦ אמורי /አሞሪ/) በጥንት ከኤፍራጥስ ወንዝ ወደ ምዕራብ የኖረ ሕዝብ ነበረ።
«የማርቱ አገር» ከሁሉ ጥንታዊ በሆኑት ሱመራዊ ምንጮች ለምሳሌ በኤንመርካርና የአራታ ንጉሥ ወይም በኤብላ ጽላቶች ይጠቀሳል። ለአካድ ነገሥታት ደግሞ 'ማርቱ' በአካድ ዙሪያ ከነበሩት 'አራት ሩቦች' አንዱ ሲሆን ሌሎቹ 3 ሱባርቱ፣ ሱመርና ኤላም ነበሩ። ይህ ስያሜ ወደ ምዕራብ የሆኑት አገራት ሶርያና ከነዓን ይጠቀልል ነበር። የአካድ ንጉሥ ናራም-ሲን ስሜን ሶርያን ክ.በ. 2250 ገደማ ወርሮ ዘመተባቸው፤ ልጁም ሻር-ካሊ-ሻሪ እንዲህ አደረገ።
በኡር መንግሥት ዘመን በአንዳንድ ሰነድ አሞራውያን እንደ ዘላኖች ይሰደባሉ። ለምሳሌ፦
- 'ምንምን እህል የማያውቁት ማርቱ.... ምንም ቤት ወይም መንደር የማያውቁት ማርቱ፣ የተራሮች ደደቦች... ለእንጉዳይ የሚቆፈር ማርቱ... (ምድርን ለማረስ) ጉልበቱን የማይበርከክ፣ ጥሬ ሥጋ የሚበላ፣ በሕይወቱ ዘመን ቤት የሌለው፣ ከሞተ በኋላ የማይቀበር ነው'።
- 'ስንዴና እህል ያዘጋጃሉ፤ አሞራዊ ግን ምን እንዳለበት ሳያውቅ ይበላዋል!'
በኡር መንግሥት ግዜ፣ አሞራውያን በአገሩ ውስጥ በጣም በመብዛታቸው ምክንያት፣ እነሱን ለመከልከል ንጉሶቹ እንደ ሹ-ሲን ከጤግሮስና ከኤፍራጥስ መኃል ታላቅ ግድግዳ ሠርተው ነበር።
የኡር መንግሥት በኤላም እጅ በ2012 ክ.በ. ገደማ በወደቀበት ግዜ በመንግሥቱ ውስጥ የኖሩት ብዙ አሞራውያን የራሳቸውን መንግሥታት አቆሙ። 'የአሞራውያን መንግሥታት ዘመን' በሜስጶጦምያ ታሪክ ከ2000 እስከ 1600 አመታት ከክርስቶስ ልደት በፊት ነው። ዋናዎቹ አሞራውያን ሥርወ መንግሥታት በማሪ፣ በያምሐድ በቃትና፣ በአሦር (በአሞራዊው 1 ሻምሺ-አዳድ ገዥነት)፣ በኢሲን፣ በላርሳና በባቢሎን ተነሡ።
ስለ ቋንቋቸው የሴማዊ ቋንቋዎች ቤተሠብ አባል ከመሆኑና ከጥቂት ስሞች በቀር ምንም ዕውቀት አሁን የለንም። በተለይ በማሪ ጽላቶች (1800-1750 ክ.በ. ገዳማ) መካከል የተገኘ የአንዳንድ አሞራዊ ጽሑፍ በአካድኛ ተጻፈ።
'የአሞራውያን ዘመን' መጨረሻ ኬጥያውያን ባቢሎንን በ1603 ክ.በ. ገዳማ ሲያሸንፉት ነበር። ከዚያ ጀምሮ አዳዲስ ወገኖች - በተለይም ካሣውያንና ሆራውያን - በሜስጶጦምያ ተነሡ። ከዚያ በኋላ አሙሩ ሲጠቀስ ማለቱ ስሜን ከነዓን እስከ ቃዴስ ብቻ ነው።
በመጽሐፍ ቅዱስ ብሉይ ኪዳን ውስጥ 'አሞራውያን' በከነዓን ምድር የኖረ ሕዝብ ነው። በኦሪት ዘፍጥረት 10፡16 መሠረት የከነዓን ካም ልጆች ናቸው። በብዙ ጥቅሶች 'አሞራውያን' እና 'ከነዓናውያን' የሚሉት ስሞች የሚለዋወጡ ያሕል ናቸው።
ከጨው ባሕር ምዕራብ ከሆኑት ተራሮች ጀምሮ እስከ ኬብሮን ድረስ ያለው አገር ከነገለዓድና ባሳን ጋር ነበራቸው። ኢያሱ እስራኤላውያንን ወደ ከነዓን ሲመራቸው ከአሞራውያን ንጉሦች ከዐግና ከሴዎን ሠራዊት ጋር ታገለ። በሳሙኤል ዘመን ግን በእስራኤልና በአሞራውያን መካከል ሰላም ነበረ።